Sunday, July 27, 2014

ያሬድ ክብር አነሰው


ያሬድ ክብር አነሰው
ገና ጥንት ያኔ . . . . . . . ሰውም ሳይሰፍርባት አሜሪካ ታውቃ፣

ገና ጥንት ያኔ . . . . . . . . . እንዲህ ሳትሠለጥን አውሮፓም ተራቅቃ፣

ገና ጥንት ያኔ . . . . . . . . ዓለም፣ ከእንቅልፏ ሳትነቃ፣

እነ ሞዛርት እና እነ ቤትሆቨን፣ የዜማን ምልክት ገና ሳይነግሩን፣

ያሬድ አንተ ነበርክ የዜማን ቅማሬ የሠራህልን፣ . . . .

መንኮራኩር ሠርተው ጨረቃ ላይ ወጥተው፣ አፈር ስላመጡ ዓለም ተደነቀ፣]

ወሬው ተሟሟቀ፣ . . . .

ከምዕራብ ተነሥቶ ከምሥራቅ ዘለቀ፣ . . . .

ከሺ ዓመት በፊት ግን ያሬድ የተባለ አንደ ሊቅ ነበረ፣ . . . .

ጨረቃንም አልፎ ጠፈር ተሻገረ፣ . . . .

ሐኖስን ሰንጥቆ ሰማያት ውስጥ ገብቶ፣ . . . .

አስደናቂ ዜማ ከመላእክት ሰምቶ፣ . . . .

አኩስም ላይ አዜመው ከጽናጽል እና ከመቋሚያ አስማምቶ፣ . . . .

ግና ምን ያደርጋል . . . . . . . ከጨረቃ አፈር የሚበልጥ ነገር፣ . . . .

ጨረቃም ላይ ካለው የሚበልጥ ምሥጢር፣ ያሬድ ይዞ መጥቶ፣ . . . .

የሚናገር እና የሚያደንቅ ጠፍቶ፣ . . . .

ዓለም አያውቀውም አልሰማውም ከቶ፣ . . . .

ያሬድ ግን ቅዱስ ነው ያሬድ ምሁር ሊቅ፣ . . . .

ያሬድ መተርጉም ነው ምሥጢር የሚያረቅቅ፣ . . . .

ያሬድ ፈላስፋ ነው ያሬድ ባለ ቅኔ፣ . . . .

ያሬድ ባለ ዜማ የዜማው መጣኔ፣ . . . .

ያሬድ ሐጋጊ ነው ሥርዓት የሠራ፣ . . . .

ያሬድ መምህር ነው ዕውቀትን ያበራ፣ . . . .

ያሬድ ቀማሚ ነው ብሉይ ከሐዲስ፣ . . . .

ያሬድ ሰባኪ ነው ነፍስ የሚመልስ፣ . . . .

ያሬድ አመልካች ነው ኖታን የፈጠረ፣ . . . .

ያሬድ መናኒ ነው በጸሎት የኖረ፣ . . . .

እነ ቸርችል፣ ፑሽኪን እና ካኒንግሃም አደባባይ መንገድ ሲሰየምላቸው፣

ያሬድን ስላጡት አዘነ ልባቸው፣ . . . .

ነቢይ በሀገሩ አይከብርም እንዲሉ፣ . . . .

እኒህ ኢትዮጵያውያን እጅግ ይሞኛሉ፣ . . . .

የእጃቸውን ንቀው ሌላ ያከብራሉ፣ . . . .

ብለው አዘኑብን በፈጸምነው ግፍ፣ . . . .

ያሬድን ረስተን ሌላውን ስናቅፍ፣ . . . .

አይበቃም ወይ ታድያ የሞኝነት ኑሮ፣ . . . .

መቅረት አለበት ወይ ታሪኩ ተቀብሮ፣ . . . .

ይተረክ ታሪኩ ይነገር ዝናው፣ . . . .

ይጠና ይመርመር ይታወቅ ሥራው፣ . . . .

መወያያ ይሁን በየሚዲያው፣ . . . .

መማማርያ ይሁን ትውልድ ያድንቀው፣ . . . .

ያለበለዚያ ግን ያለፉትን ንቀን ወደፊት ብንሄድ፣ . . . .

እኛንም የሚንቅ ይመጣል ትውልድ . 

                              በዲ.ዳንኤል ክብረት
 
 . . .

No comments:

Post a Comment