Sunday, July 27, 2014

የክብርት እመቤታችን ተዓምር

ልመናዋ ክብሯዋ በእኛ ለዘለዓለም በእውነት ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች የክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተዓምር ይህ ነው፡

በዕለታት ባንድ ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ

እናቱን በእኔ ምክንያት ካገኙሽ ኃዘኖች ማናቸው ኃዘን ይበልጣል አላት፡፡

እመቤታችንም ፈጣሪዬ ጌታዬ ሆይ በእኔ ዘንድ እኒህ አምስቱ ኃዘኖች ይበልጣሉ አለቸው፡

ከአምስቱ አንዱ አይሁድ እንዲገድሉህ በቤተመቅደስ ስምዖን ትንቢት በተናገረ ጊዜ ነው፡፡

ሁለተኛውም ሦስት ቀን በቤተመቅደስ ፈልጌህ ባጣሁህ ጊዜ ነው፡፡

ሦስተኛውም እግርህንና እጅህን አሥረው በጲላጦስ አደባባይ የገረፉህን ግርፋት ባሰብኩ ጊዜ ነው፡፡

አራተኛውም በዕለተ ዓርብ ራቁትህን ቸንክረው በሁለት ወንበዴዎችመካከል እንደሰቀሉህ ባሰብኩ ጊዜ ነው አለችው፡፡

አምስተኛውም ወደ ሐዲስ መቃብር ውስጥ እንዳወረዱ ባሰብኩ ጊዜ ነው፡፡

ጌታችንም እናቱን ድንግል ማርያምን በእኔ ምክንያት ያገኙሽን እኒህን ኃዘኖችና መከራዎች በሰላመ ገብርኤልና አቡነ ዘበሰማያትን እየደገመ ያሰበውን ኃጢአቱን እኔ አስተሰርይለታለሁ፡፡ መንግሥተ ሰማያትንም አወርሰዋለሁ አላት፡፡

እናቴ ሆይ ከሞቱ አስቀድሞ በሦስተኛው ቀን ካንቺ ጋር መጥቼ እገለጽለታለሁ፡፡ ይህን ሲናገር ቅዱስ ደቅስዮስ ሰምቶ ምእመናን ያነቧት ዘንድ በእመቤታችን ተዓምር መጽሐፍ ውስጥ ጻፈው፡፡

ልመናዋ ክብሯዋ የልጅዋ ቸርነት በእኛ ለዘለዓም በእውነት ይደርብን

No comments:

Post a Comment